ኢልሃን ኦማር ኢትዮጵያን በተመለከተ ንግግር ባደረገችበት መድረክ በሰነዘረችው አስተያየት ከአሜሪካ እንድትባረር ተጠየቀ


የአሜሪካዋ ፍሎሪዳ ግዛት አስተዳዳሪ እና ተጽዕኖ ፈጣሪው ፖለቲካኛ ሮን ዲሳንቲስ ትውልደ ሶማሊያዊቷ ኢልሃን ኦማር ዜግነቷን ተነጥቃ ከአገር እንድትባረር ጠየቁ።

ሮን ዲሳንቲስ የአሜሪካ የኮንግረስ አባሏ ኢልሃን ኦማር ከአገር እንድትባረር የጠየቁት ፖለቲከኛዋ በአንድ የሶማሊያ ማኅበረሰብ መሪዎች ስብሰባ ላይ ያደረገችውን ንግግር ተከትሎ ነው።

የዲሞክራቲክ ፓርቲ አባል እና የሜኒሶታ ግዛት ተወካይ የሆነችው ኢልሃን አነጋጋሪ የሆነውን ንግግር ያደረገችው ባለፈው ቅዳሜ ከሶማሊያ ማኅበረሰብ መሪዎች ጋር በአንድ ሆቴል ውስጥ በተደረገ ስብሰባ ላይ ነበር።

በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በስፋት ተዘዋውሮ መነጋገሪያ በሆነው ንግግሯ ከአንድ ወር በፊት ከሶማሊያ ነጻ አገርነቷን ያወጀችው ሶማሊላንድ ከኢትዮጵያ ጋር የባሕር በርን በተመለከተ የደረሰችውን ስምምነት በመቃወም ሃሳቧን ሰንዝራለች።

ኢልሃን የሶማሊያን ጥቅም ለማስከበር በአሜሪካ ምክር ቤት ውስጥ ያላትን ቦታ በመጠቀም አስፈላጊውን ሁሉ እንደምታደርግ ተናግራ፤ “ከልጆቻችሁ አንዷ በኮንግረስ ውስጥ የእናንተን ጥቅም ለመወከል ትገኛለች። በአሜሪካ ምክር ቤት ውስጥ እስካለሁ ድረስ ሶማሊያ ስጋት አይገጥማትም፣ የባሕር በሯ በኢትዮጵያም ሆነ በሌላ የአይወሰድም. . .” ስትል ተደምጣለች።

ኢልሃን በንግግሯ “መጀመሪያ ሶማሌ ነኝ በቀመጠል ሙስሊም” ብላ መናገሯ አሜሪካውያን ፖለቲከኞችን የበለጠ ያበሳጨ ሆኗል።

በቅርቡ ሪፐብሊካን ፓርቲን ወክለው ፕሬዝዳንታዊ ዕ ሆነው ከዶናልድ ትራምፕ ጋር ሲፎካከሩ የነበሩት ዲ ሳንቲስ የኢላን ኦማርን ንግግር ተከትሎ በኤክስ ገጻቸው ላይ እንዳሰፈሩት “ከኮንግረስ ተሰናብታ፣ ዜግነቷን ተነጥቃ ከአገር ትባረር!” ሲሉ ጠይቀዋል።

ከዲሳንቲስ በተጨማሪ የኮንግረስ አባሏ ማርጆሪል ግሪን “ለአሸባሪዎች ሐዘኔታ ያላት ናት” ሲሉ ኢልሃን ኦማር የወቀሱ ሲሆን፣ የትራምፕ ልጅ ዶናልድ ትራምፕ ጁኒየር ደግሞ ኢልሃን “ለሶማሊያ እና ለእስልምና ቅድሚያ በመስጠቷ አሜሪካ አጀንዳዋ አይደለችም” ብለዋል።

ኢልሃን ከሪፐብሊካን ፓርቲ መሪዎች እና ደጋፊዎች ጋር ከዚህ ቀደም ተደጋጋሚ ውዝግብ ውስጥ ስትገባ ቆይታለች። 

ኢልሃን በተለይ ከቀድሞው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጋር ተደጋጋሚ እሰጣ ገባ ውስጥ ትገባ የነበረ ሲሆን፣ ትራምፕን “አገሪቷን እንደ ስምንት ዓመት ሕፃን እየመሯት ነው” ስትል ወርፋቸው ነበር።

ኢልሃን ይህን አስተያየት የሰጠችው ትራፕም በምርጫ ቅስቀሳ ላይ ስደተኛ መሆኗን እና የመጣችበትን አገር ለማስታወስ “አገራችንን እንዴት መምራት እንዳለብን ልትነግረን ትፈልጋለች። ለመጣሽበት አገር ምን አደረግሽ? አገርሽ እንዴት ናት?” ካሉ በኋለ ነው። 

ሙስሊምና ስደተኛ ጠል የሆኑ ቀኝ አክራሪ የትራምፕ ደጋፊዎችም በፖለቲካዊ ሰልፎች ላይ ኢልሃንን “ወደመጣችበት መልሷት” የሚሉ መፈክሮችን ሲያሰሙ ነበር። 

ኢልሃን ወንድሟን አግባታለች ተብላ በኤፍቢአይ ምርምራ ተደርጎባት ነበር። 

ከጥቂት ወራት በፊት ደግሞ ዴሞክራቷ ኢልሃን እስራኤልን የተመለከተ “ልተገባ አስተያየት” ሰጥታለች ተብላ ቁልፍ ከሆነ የአሜሪካ ምክር ቤት የውጭ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ አባልነት በሪፐብሊካኖች ተባራ ነበር።

ኢልሃን ኦማር በ2019 እስራኤል የአሜሪካንን ፖለቲካ በገንዘብ ኃይል እንደምትዘውር የሚያመላክት አስተያየት ከሰጠች በኋላ ናንሲ ፔሎሲ እና ሌሎች ዲሞክራቶች ሳይቀር ከፍተኛ ትችት ሰንዝረውባት ነበር።

ኢልሃን ኦማር በበኩሏ እርምጃው አንድም ሙስሊም ሴት በመሆኔ፣ እንዲሁም ወደ አሜሪካ ምድር በስደተኝነበት በመምጣቴ የተቃጣብኝ ነው ብላ ተቃውማዋለች።

ውልደቷ በሶማሊያ ሞቃዲሾ የሆነው ኢልሃን ኦማር በስደት ወደ አሜሪካ የገባችው በአውሮፓውያኑ 1990ዎቹ መጀመሪያ ነበር።

ኢልሃን በ2016 (እአአ) በአሜሪካ በምክር ቤት አባልነት ለመመረጥ ከቻሉ የመጀመሪያዎቹ ሙስሊም አንዷ ለመሆንም በቅታለች።