በጃፓን የበረራ አስተናጋጇ በሰከረ መንገደኛ መነከሷን ተከትሎ በረራ ተቋረጠ


ተጠርጣሪው የሆነውን ሁሉ እንደማያስታውስ ለፖሊስ ተናግሯል።

ጃፓን ከሰሞኑ ከበረራ ጋር የተያያዘ ተደጋጋሚ እክሎች እያጋጠሟት ይገኛል 

የበረራ አስተናጋጇ በሰከረ መንገደኛ መነከሷን ተከትሎ በረራ ተቋረጠ፡፡

የጃፓኑ ኦል ኒፖን አየር መንገድ ከቶኪዮ ወደ አሜሪካ እየበረረ እያለ አንድ መንገደኛ በበረራ አስተናጋጇ ላይ ጉዳት አድርሷል ተብሏል፡፡

የ55 ዓመቱ አሜሪካዊ መንገደኛ የበረራ አስተናጋጇን እጅ መንከሱን ተከትሎ አውሮፕላኑ በረራውን በማቋረጥ ተመልሶ ቶኪዮ ሀኔዳ ኤርፖርት ለማረፍ መገደዱ ተገልጿል፡፡

ክስተቱ ሲፈጠር አውሮፕላኑ የፓስፊክ ውቂያኖስን እያቋረጠ ነበር የተባለ ሲሆን ረጅም ርቀት ቢጓዝም ወደ ጃፓን ሊመለስ ችሏል፡፡

በበረራ አስተናጋጇ ላይ ጉዳት አድርሷል የተባለው ተሳፋሪም ለጃፓን ፖሊስ ተላልፎ የተሰጠ ሲሆን መንገደኛው የእንቅልፍ ኪኒን ወስዶ እንደነበር እና ምን እንደተፈጠረ እንደማያስታውስ ተናግሯል ተብሏል፡፡

159 መንገደኞችን ያሳፈረው ይህ አውሮፕላን ጉዳት ለደረሰባት የበረራ አስተናጋጅ የህክምና ድጋፍ ከተደረገላት እና ጉዳት ያደረሰውን ተሳፋሪ ለፖሊስ አሳልፎ ከሰጠ በኋላ አቋርጦት የነበረውን በረራ እንዳከናወነ ተገልጿል፡፡

ጃፓን ከሰሞኑ ከበረራ ጋር የተያያዙ ተደጋጋሚ አደጋዎች ያጋጠማት ሲሆን በሁለት ሳምንት ውስጥ አምስት ከበረራ ጋር የተያያዙ ክስተቶች ተስተናግደዋል፡፡

ይሄው ኦል ኒፖን አየር መንገድ የሀገር ውስጥ በረራ እያደረገ እያለ የቦይንግ ሰራሽ አውሮፕላን መስኮት መገንጠሉ ለቀናት ዓለም አቀፍ ትኩረትን የሳበ ጉዳይ ሆኖ አልፏል፡፡

እንዲሁም 379 መንገደኞችን የጫነ ሌላ አውሮፕላን ኤርፖርት ውስጥ ከነበረ ሌላ አውሮፕላን ጋር ተጋጭቶ እሳት አደጋ ያጋጠመ ሲሆን ስድስት ተሳፋሪዎች ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡

ንብረትነቱ የኮሪያ አየር መንገድ የሆነ አውሮፕላን በሰሜናዊ ጃፓን መስመሩን በመሳቱ ምክንያት ቀላል አደጋ ያጋጠመው ሲሆን የተጎዱ ሰዎችም እንደሌሉ ተገልጿል፡፡

ባሳለፍነው እሁድም የጃፓን አየር መንገድ አውሮፕላን በአሜሪካዋ ቺካጎ ኤርፖርት ውስጥ ከዴልታ አየር መንገድ አውሮፕላን ጋር ንኪኪ ፈጥረው ነበርም ተብሏል፡፡