የሶማሊያ ፕሬዝዳንት የኢትዮጵያና የሶማሌላንድን ወደብ ስምምነት የሚያፈርስ ህግ ፈረሙ


የሶማሊያ ፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ መሐመድ፣ የተነገነጠለችው ሶማሌላንድ እራሷን የቻለች ሀገር ሆና እውቅና ለማግኘት፣ ኢትዮጵያ የቀይ ባህር ወደብ እንድታገኝ የፈፀመችውን ስምምነት የሚያፈርስ ህግ ቅዳሜ ምሽት ፈርመዋል። 

የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የቀይ ባህር ላይ ወደብ ለማግኘት ያላቸው ፍላጎት፣ በአፍሪካ ቀንድ ሀገራት መካከል አዲስ ግጭት እንዳያስነሳ ስጋት ፈጥሯል። 

ወደ አልባ የሆነችው ኢትዮጵያ ከሶማሌላንድ ጋር የፈፀመችው ስምምነት፣ ኢትዮጵያ 20 ኪሎሜትር ርዝመት ያለው የባህር ጠረፍ ለ50 አመታት እንድትከራይ እና ለንግድ እና የጦር ሰፈር አገልግሎት እንድትጠቀም የሚፈቅድ ነው። ሶማሌላንድን የሀገሯ አካል አርጋ የምትቆጥረው ሶማሊያ ግን ይህንን ስምነት ተቃውማለች። 

ፕሬዝዳንት መሐመድ "ዛሬ ምሽት፣ በኢትዮጵያ መንግስት እና በሶማሌላንድ መካከል የተደረገውን ህገወጥ የመግባቢያ ሰነድ የሚያፈርስ ህግ ፈርሜያለሁ" ሲሉ በኤክስ ወይም በቀድሞ አጠራሩ ትዊተር ላይ መልዕክት አስተላልፈዋል። 

ፕሬዝዳንቱ አክለው "ይህ ህግ በዓለም አቀፍ ህግ መሰረት አንድነታችንን፣ ሉዓላዊነታችንን እና የግዛት አንድነታችንን ለማስጠበቅ ያለንን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው" ብለዋል። 

የሶማሊያው ፕሬዝዳንት አዲሱ ህግ ምን አይነት ዝርዝሮችን እንደያዘ እና ፓርላማው መቼ እንዳፀደቀው አልገለፁም። በጉዳዩ ላይ ከኢትዮጵያም ሆነ ከሶማሌላንድ እስካሁን የተሰጠ ምላሽ የለም።